
ጌታሁን ሄራሞ
ካለፉት 4 ዓመታት ወዲህ ራሳቸውን ከጥቃት ለመከላከል አቅሙ ያላቸው ዜጎች በሕጋዊም ይሁን ሕገወጥ መንገድ የነፍስ ወከፍ መሳሪያን መታጠቅን እንደ አማራጭ እየቆጠሩ ነው። መልዕክቱ ቀላልና አጭር ነው.... ቀረጥ የምከፍልለት የፀጥታ ኃይልና መንግስት በሕይወት የመኖር መብቴን ካላስጠበቀልኝ ራሴን ከጥቃት የመከላከል ኃላፊነት እኔው ጫንቃ ላይ ወድቋል...የሚል ነው! በዚህ ረገድ ማህበራዊ ጥናት ቢደረግ ቀደም ሲል የነፍስ ወከፍ መሳሪያ ለመታጠቅ ፍላጎቱ ያልነበራቸው ሁሉ አሁን አቅማቸው ከፈቀደ መታጠቅን እንደ መፍትሔ የሚቆጥሩ ዜጎች ቁጥራቸው እያሻቀበ ስለመምጣቱ መድረስ ከባድ አይመስለኝም።
ይህ በግለሰብ ደረጃ ራስን ከጥቃት መከላከል አለፍ ሲል ወደ ቡድናዊ መከላከልም ከፍ ሊል ይችላል። በሀገሪቱ በተለያዩ ክልሎች ተሰራጭተው የሚኖሩ የብሔራቸው አባላት የሆኑ ዜጎች በሕይወት የመኖር መብታቸው በመንግስት ጥበቃ ካልተደረገላቸው ብሔር-ተኮር ቡድናዊ አደረጃጃትና ትጥቅ ሊጎለብት ይችላል..”Counter-resistance” እውን እየሆነ በሂደትም የሀገሪቱ ሰላም የሚናጋባቸው አጥቢያዎች እየሰፉ ሊመጡ ይችላሉ። ይህ ሁሉ ከሆነ በኋላ መንግስት ዜጎችን ከጥቃት ለመከላከል ባለመቻሉ የተፈጠሩ አንደንድ ቡድኖችን “ኢ-መደበኛ ታጣቂ” እያለ ቢከሳቸው ለመፈጠራቸው የራሱም አስተዋጽኦ እንዳለ መገንዘብ አለበት።
ያኔ በየክልሉ መጤ ተብለው የተፈረጁ ብሔሮች ሲገደሉና ሲፈናቀሉ መንግስት የዜጎች በሕይወት የመኖርንና ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሰው ሀብት የማፍራት ሕገመንግስታዊ መብታቸውን እንዲያስከብርላቸው ከመጮህም ባለፈ ዳተኝነቱ ከቀጠለ ሁሉም ራሱን ለመከላከል ተደራጅቶ የሀገሪቱ የፀጥታ ሁኔታ ወዳልተፈለገ አቅጣጫ ሊያመራ እንደሚችል በተደጋጋሚ ማስገንዘባችን ይታወሳል። አሁንም እንላለን፦ ዜጎች በብሔርም ሆነ በሃይማኖት ስም የሚደርስባቸውን ጥቃት መንግስት እንደአንድ ተቀዳሚ ሥራው ከመከላከል ከተቆጠበ፣ ሕዝቡ የመንግስትን ሚና ተክቶ ያዋጣኛል በሚለው መንገድ ራሱንና ቡድኑን ለመከላከል የራሱን አደረጃጃት ሊቀይስ ይችላል፤ እየቀየሰም ነው። ይህ አካሄድ ለሀገር ሰላምና ፀጥታ ፈፅሞ የሚመከር ባለመሆኑ መንግስት ሕገመንግስታዊ ግዴታውን ይወጣ፤ በገዛ ራሱ እንዝህላልነት የተፈጠሩ ታጣቂዎችን "ኢ-መደበኛ" እያለ ስያሜ ከመስጠት ይልቅ ለመፈጠራቸው አንዱም ሰበብ እራሱ መሆኑን ይገንዘብ! ገበሬው በጠብመንጃ ምትክ ማረሻውን እንዲጨብጥ መንግስት ከደህንት ስጋቱ አላቅቆት በሕይወት የመኖር መብቱን ያስከብርለት። መደበኛው ብቃት ሲያንሰው አሊያም ዳተኛ ሲሆን ኢ-መደበኛው ብቅ ማለቱ እንግዳ ክስተት አይደለም።