
✍️እስሌማን ዓባይ
የሶስቱ ምሥጢራዊ የመሳሪያ ዝውውር ሰንሰለታቸው ሲጋለጥ
የግብጹ ፕሬዚዳንት አልሲሲ፣ ከሱዳኑ ጁንታ መሪ አብዱልፈታህ አልቡርሃን እና ከደቡብ ሱዳኑ ምክትል ፕሬዚዳንት ሬክ ማቻር ጋር በፖለቲካዊ አውድ መቀራረብና መመሳጠር ከጀመሩ መሰነባበታቸው አሁን የተገለጠ ጉዳይ ሆኗል።
ከወራት በፊት በአዲስ አበባ የደቡብ ሱዳን አምባሳደር በፋና ቴሌቪዥን “ሬይክ ማቻር ያለበት አይታወቅም” ማለታቸው ይታወሳል። ከቀናት በኋላ ማቻር አለሁ የሚለው መግለጫቸው በጁባ የኢትዮጵያ አምባሳደር ጋር እንዲሁም ከውጭ ጉዳይ ከተውጣጡ ልኡካን ጋር ይፋዊ ንግግር ሲያደርጉ ታዝበናል። ከመረጃው ገረምቴነት ባለፈ አብዛኛው ሰው በተቃራኒው ከሳሽ ወገኖችን ይበልጥ እንደጠረጠራቸው ታዝቤያለሁ። ይሁን እንጂ ሁሉም የካይሮ ሲንድረም ሰለቦች ከመሆን የራቁ አልሆኑም። ጓዶች! ይህ ጉዳይ በሰዎቹ ብቻ ሳይሆን በራሴም (blind spot- የእይታ እውሬ ነጥብ) የተገረምኩበት ነገር ነው። በዚህ የሶስትዮሽ እኩይ ትያትር ውስጥ አዲሱ ገፀ ባህርይ ዶክተር ሬይክ ማቻር ሲሆን ይህ የማስነብባችሁ ስክሪፕት ደግሞ የትያትሩ ገቢር 1 (የመጀመሪያ ክፍል) ይሆናል።
ታዋቂው ግብጻዊ ፖለቲከኛ አይማን አብድልአዚዝ ኑር በአንድ ስብሰባ ባስተላለፈው መልዕክት “ኢትዮጵያ ውስጥ ኤምባሲ አያስፈልገንም። ይልቁንም በፖለቲካ እና ደህንነት ጉዳዮች ላይ የሚሰራ ግብረ ኃይል እንጂ..። እንደማስበው ስጋታችንን ለመቀልበስ በጣም አዋጭና በትንሽ ዋጋ የምናተርፍበት አማራጭ ይህ ነው፤ በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ በመግባት ሀገሪቱን ማተራመስ አለብን…ߴߴ። ማለቱን የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት መዘገቡ ይታወሳል፡፡
መሰል እሳቤዎች ከካይሮ ልሂቃን ባለፈ የሀገሪቱ ፖለቲከኞችና መንግሥት አቋም ራሱ ከዚህ የተለየ እንዳልሆነ በርካታ ተንታኞች ሲገልፁት የሚገኝ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከምትገኝበት ፈተና የከተቱን ችግሮች ከተለያዩ ምንጮች የፈለቁ መሆናቸውን ማንም የሚክደው ባይሆንም፣ ከካይሮ ፈልቆ እኛ ጋር የሚደርሰው ግን የከፋው ነውና የዚህ ክታብ ትኩረትም እዚሁ ላይ ይሆናል፤ ያውም አንዲቷ ዘለላ ብቻ፤ እንቀጥል..።
ከላይ የጠቀስኳቸው የሴረኛ ትያትሩ መሪ ተዋንያን በካይሮ ሸለምጥማጣዊ ሲንድረም ተጠልፈው ነበርና በቅርርባቸው ከፖለቲካዊው አውድ የተሻገረ ድር ሲያባዘቱበትም ነበር የባጁት ለካ። መረባቸው ከባልካን ሀገራት እስከ አፍሪካ ቀንድ የተዘረጋ የህገወጥ ጦር መሣሪያ ንግድ ሰንሰለት እስከመዘርጋት የደረሱበት ሲሆን፤ የማቀነባበርና የመምራት ተግባራቸው በምስጢራዊ መረጃዎች ተደራጅቶ (በከፊልም ቢሆን) እውነታው እንዲህ ይፋ ለመሆን በቅቷል። ከሰሞኑ ይፋ ተደርጓል፡፡
ሳምንታት ብቻ ወደ ኋላ ተመልሰን ጋምቤላ ስላስተናገደችው አሳዛኝ ጥቃት ብናወሳ፣ ስለ ግድቡ ዜጎቻቸውን “አታስቡ” በማለት ውስጥ ለውስጥ ስራቸውን እየሰሩ መሆናቸውን በጠቆሙበት ንግግራቸው ፕሬዝደንት አልሲሲ “ስለ ናይል ውሃ መብታችን አትጨነቁ። ወሬውን አቁመን ስራችንን እየሰራን ነው።” ማለታቸውን የግብፁ ዴይሊ ኒውስ አስነብቦን ነበር። ጊዜው ደግሞ june 13 ነበር። በቀጣዩ ቀን ጁን 14 በጋምቤላ የሆነው ሁሉ ጥቃት እንዲፈፀም ሆነ።




የቀጣናውን ጂኦፖለቲካ ጉዳዮች በቅርበት ከሚከታተሉ ምንጮች የተገኘው ምስጢራዊ መረጃ እንደሚያመላክተው፤ የሶስቱ ሀገራት አመራሮችና ወኪሎቻቸው በዚህ ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውር እጃቸውን ያስገቡት በተለያዩ መግፍኤዎች የተነሳ መሆኑን ይጠቁማል፡፡
በዋናነትም በምስራቅ አፍሪካ የተረጋጋ ማዕከላዊ መንግሥት መመስረት ያቃታቸው የሁለቱ ሱዳኖች አመራሮች በቀጣናው ቀውስን በማስፋፋት ግጭትን እንደ ስልጣን ማራዘሚያ ለመጠቀም የሚለው ሰበብ ለመሳሪያ ዝውውሩ ተዋንያን ዋነኛው መሆኑ ታውቋል፡፡ ሶስቱ አመራሮች ከጦር መሣሪያ ዝውውሩ ሊያገኙ የሚችሉት የደም ገንዘብ ሁለተኛው ያነሳሳቸው ሰበብ እንደሆነም ተደርሶበታል፡፡ ህወሓት፣ ሼኔ እና የጉሙዝ ታጣቂዎች ከግብጽ መንግሥት የስለላ መስሪያ ቤት የመሣሪያና ሎጀስቲክስ ድጋፍ በዚህ ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውር ሰንሰለት አማካኝነት በቀጥታ እንደሚደርሳቸውም ነው መረጃው የጠቆመው፡፡
መሣሪያዎቹ ለጊዜው ስማቸው እንዲገለጽ ካልተፈለጉ የባልካን ሀገራት በቀጥታ ተገዝተው በአል ሲሲ ልዩ መልእክተኞች አማካኝነት የዶክተር ሬክ ማቻር ታማኝ ታጣቂዎች ወደሚንቀሳቀሱባቸው የደቡብ ሱዳን አካባቢዎች ከተሸጋገሩ በኋላ ለተለያዩ የሽብር ቡድኖቹም እንዲደርሱ እየተደረገ መሆኑ ታውቋል። የዚህ የጥፋት ሰንሰለት ተዋንያት ዘንድ የሚዘዋወሩ ህገ ወጥ የጦር መሳሪያዎች ለራሳቸው የጥፋት ተግባር እንዲሁም በቀጣናው ለሚንቀሳቀሰው የአልሸባብ ክንፍ ለማስተላለፍም የተለያዩ ኮሙኒኬሽኖችን ስለማድረጋቸውም መረጃዎችም መገኘታቸውን ነው ምንጮቹ ያስቀመጡት፡፡
ግብፅ በያዝነው አመት በኢትዮጵያ የኮፕቲክ/ኦርቶዶክስ ክርስትናን እና እስልምናን ከህዳሴ ግድቡ እና ከህወሃት ጋር ተያያዥ ፖለቲካዊ ጫና መፍጠሪያነት ለመጠቀም ስራ መጀመሯን የገለፀችው በይፋ ሲሆን እነ አሕራም ኦንላይን በፊት ገፃቸው ያስነበቡን እውነታ ነው። ካይሮ በወቅቱ በይፋ የነገረችንን ያላነበባችሁ ካላችሁ (ከታች ባለው ሊንግ አግኙት)፤ ያልነገረችንን ደግሞ በሴረኛው ትያትሯ እየተመለከትነው እንገኛለን።
ሰላም ለሀገራችን
የዓባይልጅ Esleman Abay #GERD
Read more & check sources ⬇️
🔹shorturl.at/nyP78
🔹shorturl.at/aeqzC
Twitter ⬇️
🔹https://twitter.com/eslemanabayy?t=skbhVBbI2I1QIvyXuxwA_g&s=09
1 thought on “ሬክ ማቻር እና አልቡርሃን የአል-ሲሲ ሴረኛ ትያትር ተዋንያን”
በሀገራችን የአባይ ጉዳይ በምታቀርባቸው ጽሁፎች፣ ለኢትዮጵያ መብትና ጥቅም ለምታደርገው ትግል ትልቅ አድናቆት አለኝ። በተለይም የጥናታዊ ጽሁፍ ሚና ወሳኝ ነው።