
በውብሸት ሙላት
የዚህ ታሪክ መነሻ ሐሳብም መረጃም የተወሰደው “የተካደው የሰሜን ዕዝ” ከሚለው ከጋሻው ጤናዬ (ቻቻው) መጽሐፍ፣ ከገጽ 274 እስከ 279፣ ነው።
ቻቻው ታጋች ነበር። እሱና ጓዶቹ በታገቱ በ25ኛ ቀናቸው ነው የተለቀቁት። ከመጹሐፉ እንደምናገኘው፣ ከሌሊቱ 5፡00 ከአቢይ አዲ በመኪና ተጭነው ከ 4 ሰዓታት የስቃይ ጉዞ በኋላ 9፡00 ሲኾን መኪናው ተንቤን በርሃ ውስጥ ከተራሮች ግርጌ ላይ መኪናው አራግፏቸው ተመለሰ። ፒስታው መንገድ አልቆ አስፓልት ሲጀምር ነው ያራገፋቸው። በእግራቸው 1 ኪሜ የሚረዝም አስፓልት ተጓዙ።

ከዚያ አስፓልቱ አለቀ። አስፓልቱ ለዋሻ አቀበላቸው። በዋሻ ውስጥ ለ 30 ደቂቃ ተጓዙ። 3 ኪሜ የሚሆን ዋሻ። ጉዞው ድቅድቅ ባለ ጨለማ ውስጥ ነው። አንዳንድ ታጋቾች በያዟቸው ባቲሪዎች እርዳታ ማየት እንደቻለው የሚዘግብልን ደራሲው፤ ዋሻው አስፓልት ነው። በወቅቱ ባይበራም በውስጡ ኤሌክትሪክ አለ። ከዋሻው ውስጥ ወደ ግራ አቅጣጫ የሚገቡ ሌሎች ሁለት ዋሻዎች እንዳሉ ይነግረናል። ዋሻው የሚገኘው ከተከዜ ግድብ በስተምዕራብ በኩል ነው። የእነዚህ ዋሻዎች ርዝመታቸው ምን ያህል እንደሆነም በውስጣቸው ትሕነግ ምን እየሠራችባቸው እንደሆነ፣ ምን እንደደበቀቺባቸው የሚታወቅ ነገር የለም። የኬሚካል መሣሪያ እያዘጋጀችባቸውም እንደሆነ አይታወቅም።

ከዋሻው ሲወጡ ትሕነግ የረሸነቻቸውን የአስከሬን ክምር እየረገጡ እንደወጡ ይነግረናል። ከዚያም 500 በሜትር ገደማ የሚደርስ አስቸጋሪ ቁልቁለት በእንፉቅቅ ወርደው በተከዜን ድልድይ ተሻግረው ወደ አማራ ክልል ገቡ።
እነዚህ፣ ትሕነግ ከጥቅምት 24/2013 ዓ.ም. በፊት የሠራቺው ምሥጢራዊ ዋሻዎች ናቸው። የሚገኙትም በአማራ ክልል አዋሳኝ ነው። ትሕነግ ከጥቅምት 24 በፊት ምን ሥትሠራባቸው እንደነበርና አሁንም ምን እየሠራችባቸው እንደሆነ አይታወቅም። ከመቀሌ ሲሸሹ በእነዚህ ዋሻዎች ውስጥ መሽገው ሊሆን ይችላል።
አማራ ክልል ላይ ማንኛውንም ዓይነት ጥቃት ለመፈጸም እነዚህ ዋሻዎች መንደርደሪያም መደበቂያና መሸሸጊያም እንደሚሆኑ የሚያጠራጥር አይደለም። ወደ ዋግኽምራም ወደ ጎንደርም። የፌደራሉም ይሁን የአማራ ክልል መንግሥታት እነዚህን ዋሻዎች ልዩ ትኩረት በመስጠት መከታተልና የተጠና እርምጃ ሊወሱዱባቸው ግድ ይላል።

መጽሐፉ ላይ ከቀረበው መረጃ በመነሳት፣ ከተለያዩ ካርታዎች በመጠቀም እንደተገነዘብኩት የዋሻው መግቢያና መውጪያ ከታች ባያያዝኳቸው ምስሎች የሚታው ነው። በቀይ ቀለም ምልክት ያደረግኩባቸው መግቢያና መውጫው ናቸው።